'ተዓምራዊ' የተባለው ከሞተች ሴት በተለገሰ ማሕጸን የተወለደው የመጀመሪያው ሕጻን
Author
amc-admin
Date Published

'ተዓምራዊ' የተባለው ከሞተች ሴት በተለገሰ ማሕጸን የተወለደው የመጀመሪያው ሕጻን
ግሬስ ቤል በ30ዎቹ ዕድሜ ክልል ትገኛለች። የተወለደችው ያለ ማሕጸን ነው። ግሬስ እና የፍቅር አጋሯ ስቲቭ ፖዌል ልጅ እንዲኖራቸው ይመኙ ነበር።
አሁን 'ተአምራዊ' ልጅ አግኝተዋል። ከዚህ ዓለም በሞት ከተለየች ሴት በተለገሰ ማሕጸን ልጃቸው ሁጎ ተወልዷል።
ሁጎ ከተወለደ 10 ሳምንቱ ነው። ግሬስ "በተአምር የተወለደ ልጅ ነው" ትላለች።
በዩናይትድ ኪንግደም ታሪክ ከሞተች ሴት በተለገሰ ማሕጸን ልጅ ሲወለድ ሁጎ የመጀመሪያው ነው።
ግሬስ እና ስቲቭ የሚኖሩት በኬንት ነው። ማሕጸኗን የለገሰችውን ሴት እና ቤተሰቦቿን ያመሰግናሉ።
"በጣም ደግ እና ለሰዎች የምታስብ" ሲሉ ለጋሿን ያሞካሻሉ። ቤተሰቦቿንም "ታላቅ ስጦታ ሰጥተውናል" ብለዋቸዋል።
ልጁ ሊወለድ የቻለው በኦክስፎርድ እና በለንደን በሚገኙ የሕክምና ባለሙያዎች ጥምረት ነው።
የቀዶ ሕክምና ባለሙያዎቹ ልጁ "ታሪክ የሚለውጥ ነው" ብለዋል። እንደ ግሬስ ላሉ በርካታ ሴቶች ልጅ የማግኘት ተስፋ የሚሰጥ እንደሆነም ተናግረዋል።
ሁጎ ምዕራብ ለንደን በሚገኘው ክዊን ሻርለስ ኤንድ ቸልሲ ሆስፒታል ነው የተወለደው። ሲወለድ 3 ኪሎ ግራም ነበር።
ግሬስ የተወለደችው ያለ ማሕጸን ስለሆነ የወር አበባ አታይም። ይህ ሁኔታ ኤምአርኬኤች (MRKH syndrome) ይባላል። በዩናይትድ ኪንግደም ብቻ 5,000 ሴቶች ተመሳሳይ እክል ይገጥማቸዋል።
ግሬስ ልጅ መውለድ እንደማትችል የተነገራት በ16 ዓመቷ ነበር።
#BBC

